ልደተ ክርስቶስ

 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አኃዱ አምላክ፤ አሜን።

የሰው ልጅ የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ተላልፎ በሐጢያት ከወደቀ በኋላ እግዚአብሔር ወደ ቀደመ ክብሩና ቦታው ይመልሰው ዘንድ በንሰሐ ወደፈጣሪው ቀረበ። አዳም እና ሔዋን ከገነት ከወጡ በኋላ ለአርባ ቀናት ያህል ሱባዔ ገብተው ሳለ በ35 ኛው ቀን ከግማሽ ላይ ቀድሞ የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ እንዲያፈርሱ ያደረጋቸው ሰይጣን ዳግመኛ ወደ ሔዋን ቀርቦ ሔዋን ሆይ ጸሎታችሁ ተሰማ አዳምን ይዘሽ ወደዚህ ነይ አላት። እርሷም በጎ መልአክ መስሎ የቀረበውን የጥንተ ጠላታቸውን ድምጽ ሰምታ አዳምን ይዛ ከሱባኤያቸው ወጡ። በመንገድም ሲሄዱ በጎ መልአክ መስሎ የመጣው ዲያብሎስ አሁን አገኘሁህ ከኔ አታመልጥም ብሎ አዳምን ድንጋይ አንስቶ ፈነከተውና ተሰወረ።

አዳምም በወደቀበት ደሙን እያዘራ ምርር ብሎ በማልቀስ ከዋለ ካደረ በኋላ እውነተኛው መልአክ ቅዱስ ገብረኤል ተገልጾ አጽናናው። ፈጣሪ አምላክም የደረሰበትን ሁሉ አይቶ አዘነለት። ከወደቀበት መከራም ሁሉ ያድነው ዘንድ ወዶ የተስፋ ቃል ሰጠው። ይህም የተስፋ ቃል ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ መጥቼ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለው የሚል ነበረ።

መልአኩም ቅዱስ ገብርኤል በል ተነስተህ ሔዋንን ያዝና ሂድ ብሎ አዘዘው። አዳም ግን ይህች ሴት ሁለት ጊዜ ከፈጣሪዬ አጣላችኝ ከዚህ በኋላ ላያት አልፈልግም ብሎ እምቢ አለ። መላኩም አዳም ሆይ ከወጣህበት ገነት የምትመለሰው ድህነትንም የምታገኘው በእርሷ በኩል ነውና ሔዋንን ይዘህ ሂድ አለው። በዚህም ለሰዎች ድኅነትን የምታሰጥ የመድኃኒታቸው መገኛ የሆነች ዳግማዊት ሄዋን የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የድህነታች መሠረት እንደሆነች ታወቀ።

ዳግመኛም አምላክ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለው ያለውን የተስፋ ቃል አዳም በልቡ ሰንቆ መኖሩ ያቺ የተስፋው ቃል ድንግል ማርያም እንደሆነች የተረዳ ነገር ሆነ። ሊቁ “አንቲሁ ተስፋሁ ለአዳም አመ ይሰደድ እምገነት” በማለት እንደተናገረው ከገነት በተሰደደ ጊዜ ለአዳም ተስፋው የሆነች ድንግል ማርያም ናትና።

እንግዲህ ይህ የዘመን ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ የሰው ልጆችን ሊያድን ጌታችን እና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ።

ከመወልዱ አስቀድሞ ከተወለደም በኋላ በምን ሁኔታ እንደሚጸነስ እና የት፣ ከማን፣ እንደምን ባለ ሁኔታ እንደሚወለድ በአበውና በነብያት እንዲሁም በሃዋርያት መጽሐፍት ውስጥ ታርኩ በሰፊው ተመዝግቦ ይገኛል። ከእነኝህ የመጽሐፍት ክፍሎች ውስጥ አብዛኛውን ለአንባብያን በመተው ጥቂቶቹን ብቻ እንደሚከተለው እንመለከታለን።

በብሉይ ኪዳን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ/ሰው መሆን የተነገሩ ኃይለ ቃላት  

  1. ኦሪት ዘፍ. 22:8,13 “አብርሃምም። ልጄ ሆይ፥ የመሥዋዕቱን በግ እግዚአብሔር ያዘጋጃል አለው፤ ሁለቱም አብረው ሄዱ። … አብርሃምም ዓይኑን አነሣ፥ በኋላውም እነሆ አንድ በግ በዱር ውስጥ ቀንዶቹ በዕፀ ሳቤቅ ተይዞ አየ፤ አብርሃምም ሄደ በጉንም ወሰደው፥ በልጁም ፋንታ መሥዋዕት አድርጎ ሠዋው።”
  2. ትንቢተ ሚል. 5:2 “አንቺም ቤተ ልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል።”
  3. ትንቢተ ኢሳ. 11:1 “ከእሴይ ግንድ በትር ይወጣል፥ ከሥሩም ቍጥቋጥ ያፈራል።”
  4. ትንቢተ ኤር. 23:5 “ እነሆ፥ ለዳዊት ጻድቅ ቍጥቋጥ የማስነሣበት ዘመን ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር፥ እርሱም እንደ ንጉሥ ይነግሣል፥ ይከናወንለታልም፥ በምድርም ፍርድንና ጽድቅን ያደርጋል።”
  5. ትንቢተ ኢሳ. 7:14 “ስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፤ እነሆ፥ ድንግል ትፀንሳለች፥ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፥ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች።”
  6. መዝ. 72:9-10 “በፊቱም ኢትዮጵያ ይሰግዳሉ፥ ጠላቶቹም አፈር ይልሳሉ። የተርሴስና የደሴቶች ነገሥታት ስጦታን ያመጣሉ፤ የዓረብና የሳባ ነገሥታት እጅ መንሻን ያቀርባሉ።”
  7. መዝ. 2:7 “ትእዛዙን እናገራለሁ፤ እግዚአብሔር አለኝ። አንተ ልጄ ነህ፥ እኔ ዛሬ ወለድሁህ።”
  8. መዝ. 9:2,6 “ በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን አየ፤ በሞት ጥላ አገርም ለኖሩ ብርሃን ወጣላቸው። …. ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል።”

በአዲስ ኪዳን ስለ ክርስቶስ መወለድ/ ሰው መሆን የተጻፉ፦ 

  1. ማቴ. 1:1 “ የዳዊት ልጅ የአብርሃም ልጅ የኢየሱስ ክርስቶስ ትውልድ መጽሐፍ”
  2. ማቴ. 1:18 “ የኢየሱስ ክርስቶስም ልደት እንዲህ ነበረ። እናቱ ማርያም ለዮሴፍ በታጨች ጊዜ ሳይገናኙ

ከመንፈስ ቅዱስ ፀንሳ ተገኘች”

  1. ማቴ. 1፡20-23 “እርሱ ግን ይህን ሲያስብ፥ እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ታየው፥ እንዲህም አለ። የዳዊት ልጅ ዮሴፍ ሆይ፥ ከእርስዋ የተፀነሰው ከመንፈስ ቅዱስ ነውና እጮኛህን ማርያምን ለመውሰድ አትፍራ።… ልጅም ትወልዳለች፤ እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ። እነሆ፥ ድንግል ትፀንሳለች ልጅም ትወልዳለች፥ ስሙንም አማኑኤል ይሉታል የተባለው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሁሉ ሆኖአል፥ ትርጓሜውም። እግዚአብሔር ከእኛ ጋር የሚል ነው። ”
  1. ማቴ.2:1-2 “ኢየሱስም በይሁዳ ቤተ ልሔም በንጉሡ በሄሮድስ ዘመን በተወለደ ጊዜ፥ እነሆ፥ ሰብአ ሰገል። የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው? ኮከቡን በምሥራቅ አይተን ልንሰግድለት መጥተናልና እያሉ ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም መጡ።”
  2. ሉቃ.1 30-33 ” መልአኩም እንዲህ አላት። ማርያም ሆይ፥ በእግዚአብሔር ፊት ጸጋ አግኝተሻልና አትፍሪ። እነሆም፥ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፥ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ። እርሱ ታላቅ ይሆናል የልዑል ልጅም ይባላል፥ ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፤ በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘለላም ይነግሣል፥ ለመንግሥቱም መጨረሻ የለውም።”
  3. “ ይህም ከላይ የመጣ ብርሃን በጐበኘበት በአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ምክንያት ነው፤

ብርሃኑም በጨለማና በሞት ጥላ ተቀምጠው ላሉት ያበራል እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናል”

  1. ሉቃ. 2:6-14 “ በዚያም ሳሉ የመውለጃዋ ወራት ደረሰ፥ የበኵር ልጅዋንም ወለደች፥ በመጠቅለያም ጠቀለለችው፤ በእንግዶችም ማደሪያ ስፍራ ስላልነበራቸው በግርግም አስተኛችው። በዚያም ምድር መንጋቸውን በሌሊት ሲጠብቁ በሜዳ ያደሩ እረኞች ነበሩ። እነሆም፥ የጌታ መልአክ ወደ እነርሱ ቀረበ የጌታ ክብርም በዙሪያቸው አበራ፥ ታላቅ ፍርሃትም ፈሩ። መልአኩም እንዲህ አላቸው። እነሆ፥ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፤ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና። ይህም ምልክት ይሆንላችኋል፤ ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግምም ተኝቶ ታገኛላችሁ። ድንገትም ብዙ የሰማይ ሠራዊት ከመልአኩ ጋር ነበሩ። እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ። ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ አሉ።”
  2. ገላ. 4:4 “ ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ፤” 

ወዳጆች ሆይ፤ እኒህን ሁሉ የእግዚአብሔር ቃሎች አምነን የጌታን ልደት ስናከብር ድርሻችን ታሪኩን ማወቅና በእግዚአብሔር ልጅ ማመን ብቻ ሳይሆን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ወዚህ ዓለም የመጣበትን ዋነኛውን ዓላማ ፈጽመን እንድንገኝም ጭምር ነው። ይኽውም ከሃጢያትና በደል እርቀን ብርሃን የሆነንን ክርስቶስን ለብሰን ዘወትር ዝግጁ በመሆን የዘላለም ሕይወትን ለመውረስ የበቃን እንድንሆን ነው። የጌታን ልደት የምናከብርበት የገና በአል ዘወትር በየአመቱ ሲመላለስ እኛም ዘወትር በንሰሐ እየታደስን በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ በመወሰን አዲስ ሕይወትና አዲስ መንፈስ ሊኖረን ይገባል። ነብዩ ““ አዲስ ልብና አዲስ መንፈስ ለእናንተ አድርጉ :: ብሎ እንደነገረን  ” ሕዝ. 18፥31

መልካም በአል።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክብር።